cookie

نحن نستخدم ملفات تعريف الارتباط لتحسين تجربة التصفح الخاصة بك. بالنقر على "قبول الكل"، أنت توافق على استخدام ملفات تعريف الارتباط.

avatar

ዋዜማ ሬዲዮ - Wazema Radio

إظهار المزيد
مشاركات الإعلانات
1 721
المشتركون
+1124 ساعات
+67 أيام
+1630 أيام

جاري تحميل البيانات...

معدل نمو المشترك

جاري تحميل البيانات...

Photo unavailableShow in Telegram
በደቡብ ጎንደር ዞን በሚገኙ ከአምስት ወረዳዎች ከ2016 ዓ.ም ማብቂያ ጀምሮ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ለቀው መውጣታቸውን ዋዜማ ተረድታለች። የመንግስት ኃይሎች ለምን ከአካባቢው እንደወጡ በይፋ አልተናገሩም። አንብቡት-https://tinyurl.com/avw5rdu8 📷 FILE
إظهار الكل...
ለቸኮለ ማለዳ! ሐሙስ መስከረም 9/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ የፋኖ ታጣቂዎች በደቡብ ጎንደር ዞን አምስት ወረዳዎችን እንደተቆጣጠሩ ዋዜማ ካሰባሰበቻቸው መረጃዎች ተረድታለች። ፖሊሶች፣ ሚሊሻዎችና የወረዳና ቀበሌ አመራሮች ወረዳዎቹን ለቀው ከዞኑ ዋና መቀመጫ ደብረታቦር ገብተዋል። የፋኖ ታጣቂዎች ከጳጉሜ መጨረሻ ጀምሮ ባሉት ቀናት በተቆጣጠሯቸው ታች ጋይንት፣ እስቴ፣ አንዳቤት፣ መካነእየሱስ፣ ስማዳ እና ስዴ ሙጃ ወረዳዎች፣ የራሳቸውን አስተዳደራዊ መዋቅሮች የመዘርጋትና ግብር የመሰብሰብ ሙከራ እያደረጉ እንደኾነም ዋዜማ ሰምታለች። link- https://tinyurl.com/avw5rdu8 2፤ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳን ጨምሮ ከሕወሓት ጉባዔ ራሳቸውን ያገለሉ 16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ ደብረጺዮን ገ/ሚካዔል የሚመሩት ቡድን በጊዜያዊ አስተዳደሩ ላይ መፈንቅለ ሥልጣን ለማድረግ አቅዷል በማለት ከሷል። የጌታቸው ቡድን ትናንት ምሽት ባወጣው መግለጫ፣ የደብረጺዮን ቡድን ሌሎችን ከፓርቲው የማሰናበት ሕጋዊ ሥልጣንም ኾነ ሞራል የለውም በማለትም የቡድኑ አባላት ከፓርቲው ስለመባረራቸው የተላለፈውን ውሳኔ አጣጥሏል። የደብረጺዮን ቡድን፣ በትግራይ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንዳልተፈጸመ ጭምር በመካድ በትግራይ ሕዝብ ላይ ተደጋጋሚ ክህደቶችን እየፈጸመ ይገኛል በማለት ይሄው ቡድን ወቅሷል። ቡድኑ፣ የሕወሓትን ሕጋዊ ሰውነት ለማስመለስ አደርገዋለሁ ባለው ፓለቲካዊ ድርድር፣ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ከጎኑ እንዲቆሙም ጥሪ አድርጓል። 3፤ በሶማሌ ክልል ዋርዴር ከተማ ውስጥ ባንድ መስጊድ ላይ ትናንት በተፈጸመ ጥቃት ስድስት ሰዎች እንደተገደሉ ከነዋሪዎችና ባለሥልጣናት መስማቱን ጠቅሶ ቪኦኤ ዘግቧል። በጥቃቱ የተገደሉት፣ የእስልምና ሃይማኖት ተማሪዎች እንደኾኑ ዘገባው አመልክቷል። ጥቃቱን የፈጸሙት፣ የፖለቲካ አጀንዳ ያላቸው ግለሰቦች ናቸው በማለት የአካባቢው ባለሥልጣናት መናገራቸውንና በቅርቡ ባካባቢው ተከስቶ ከነበረ የጎሳ ግጭት ጋር የተያያዘ አይደለም የሚል እምነት እንዳላቸው መግለጣቸውን ዘገባው አመልክቷል። የክልሉ መንግሥት፣ በመስጊዱ ላይ ተፈጸመ ስለተባለው ጥቃትና ሰዎች ተገድለዋል ስለመባሉ በይፋ ያለው ነገር የለም። 4፤ ራስ ገዙ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ በ2016 የትምህርት ዘመን በተሰጠው የ12ኛ ክፍል አገር ዓቀፍ ፈተና ከ500 እና ከዚያ በላይ ነጥብ ያስመዘገቡ 200 ተማሪዎችን አወዳድሮ ነጻ የትምህርት ዕድል ለመስጠት መወሰኑን አስታውቋል። ዩኒቨርሲቲው፣ 200 ተማሪዎችን ለመምረጥ የመግቢያ ፈተና እንደሚሰጥና ብቃትን፣ ብዝሃነትንና ፍትሃዊነትን ማዕከል አድርጎ ከፍተኛ ውጤት ያመጡትን እንደሚቀበል ገልጧል። ዩኒቨርሲቲው ነጻ የትምህርት ዕድል ለሚሰጣቸው ተማሪዎች የመኝታና የምግብ አገልግሎት ጭምር እንደሚሰጥ አመልክቷል። 5፤ የተመድ ጠቅላላ ጉባዔ፣ እስራኤል በኃይል የያዘቻቸውን አካባቢዎች ባንድ ዓመት ውስጥ እንድትለቅ ትናንት በድምጽ ብልጫ ባሳለፈው ውሳኔ ላይ ኢትዮጵያ ድምጸ ተዓቅቦ አድርጋለች። ጠቅላላ ጉባዔው ውሳኔውን ያሳለፈው፣ በ124 የድጋፍ ድምጽ ነው። አሜሪካን ጨምሮ 12 አገራት የተቃውሞ ድምጽ ሲያስመዘግቡ፣ 43 አገራት ደሞ ድምጸ ተዓቅቦ አድርገዋል። እስራኤል በወረራው ሳቢያ በፍልስጤማዊያን ላይ ላደረሰችው ጉዳት ካሳ እንድትከፍል ጭምር ጠይቋል። በእስራኤል ወረራ ሥር የሚገኙት፣ ዌስት ባንክና ምሥራቅ እየሩሳሌም ናቸው። የተመድ ጠቅላላ ጉባዔ ውሳኔ አስገዳጅነት የለውም። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 2
*በአማራ ክልል ለ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ይመዘገባሉ ተብሎ ከታቀደው 7 ሚሊዮን ተማሪዎች ውስጥ እስካሁን የተመዘገቡት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ተማሪዎች ብቻ ናቸው። *ዋዜማ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ባደረገችው ማጣራት በ2016 የትምህርት ዘመን ተዘግተው የከረሙ በርካታ ትምህርት ቤቶች ለዘንድሮው የትምህርት ዘመንም እስካሁን ምዝገባ አላከናወኑም። *ክልሉ ባጋጠመው የጸጥታ ችግር ምክንያት ባለፈው ዓመት የትምህርት ዘመን ከ4 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች ሙሉ ዓመቱን ሳይማሩ አሳልፈዋል። ዝርዝሩ ይኸው- https://tinyurl.com/y262w9uy 📷 Unicef
إظهار الكل...
በአማራ ክልል 5 ነጥብ 5 ሚሊዮን ተማሪዎች ለዘንድሮው የትምህርት ዘመን አልተመዘገቡም - Wazemaradio

ዋዜማ- በአማራ ክልል ለ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ይመዘገባሉ ተብሎ ከታቀደው 7 ሚሊዮን ተማሪዎች ውስጥ እስካሁን የተመዘገቡት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ተማሪዎች ብቻ ናቸው። ክልሉ የ2017 የትምህርት ዘመንን መስከረም 7 ቀን አስጀምሯል። ሆኖም ለዘንድሮው የትምህርት ዘመን እስካሁን የተመዘገቡት 21 በመቶ ገደማ ያህሉ ብቻ መሆናቸውን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታውቋል። ዋዜማ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ባደረገችው ማጣራት በ2016 የትምህርት

ለቸኮለ ማለዳ! ረቡዕ መስከረም 8/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ በጎንደር ከተማና አካባቢዋ በመንግሥት ወታደሮችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በተቀሰቀሰው ውጊያ ሳቢያ፣ በጎንደርና ባሕርዳር እንዲሁም በጎንደር እና በወረዳ ከተሞች መካከል የትራንስፖርት አገልግሎት መቋረጡን ዋዜማ ሰምታለች። ኹለቱ ወገኖች ሰኞ'ለት በሰሜን ጎንደር ዞን ባካሄዱት ውጊያ፣ የፋኖ ታጣቂዎች ላጭር ጊዜ የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና መቀመጫ ደባርቅ ከተማን ተቆጣጥረው እንደነበር ምንጮች ተናግረዋል። በውጊያው ቁጥራቸው ያልታወቁ ሰዎች እንደተገደሉና እንደቆሰሉ ዋዜማ ካሰባሰበቻቸው መረጃዎች መረዳት ችላለች። 2፤ የሕወሓት ሊቀመንበር ደብረጺዮን ገ/ሚካዔል "ኒው ሆሪዞን" ከተባለ የበይነ መረብ ጣቢያ ጋር ሰሞኑን ያደረጉት ቃለ ምልልስ፣ በሰሜኑ ጦርነት በተገደሉ ሰዎች ዙሪያ የሰጡት አስተያየት ከቁጥር ጋር የተያያዘ ውዥንብር እንደፈጠረ መረዳታቸውን ገልጸዋል። ደብረጺዮን በቃለ ምልልሳቸው፣ በጦርነቱ 1 ሚሊዮን ሕዝብ አልቋል የሚባለው ነገር በጥናት ላይ ያልተመሠረተና ማስረጃ የሌለው አመራሩን ተጠያቂ ለማድረግ ሲባል ብቻ የሚነገር ነገር እንደኾነ ተናግረው ነበር። ኾኖም ደብረጺዮን ትናንት ምሽት ላይ በሕወሓት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ በኩል በሰጡት ማብራሪያ፣ በእያንዳንዱ የትግራይ ቤተሰብ ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንደተፈጸመ በመግለጽ የወንጀሉ ሰለባዎች ቁጥር ከዚህም ሊልቅ ይችላል ብለዋል። የዘር ማጥፋት ወንጀሉ አኹንም ቀጥሏል ያሉት ደብረጺዮን፣ በውስጣችን የሚገኙ አንዳንድ ግለሰቦች ራሳቸውን ከተጠያቂነት ነጻ ለማድረግና በዘር ማጥፋት ወንጀሉ ተጠያቂ መኾን ያለባቸው ሌሎች አካላት እንዳይጠየቁ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ በማለት ከሰዋል። ደብረጺዮን በቃለ ምልልሱ ላይ ማስረዳት የፈለጉት የእነዚህን በስም ያልጠቀሷቸው አካላት ድርጊት እንጂ በዘር ማጥፋት ወንጀሉ የጠፋውን የሰው ሕይወት ብዛት አይደለም በማለት አስተባብለዋል። 3፤ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ ወረዳ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ሁለት የመንግሥት ሠራተኞች እንደተገደሉና ሌላ አንድ የመንግሥት ሠራተኛ እንደቆሰለ ዶቸቨለ ዘግቧል። ሠራተኞቹ ጥይት የተተኮሰባቸው፣ በሞተር ሳይክል በመጓዝ ላይ ሳሉ እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። ታጣቂዎቹ ጥቃቱን ያደረሱት፣ ሦስቱ ግለሰቦች ከኪረሙ ወረዳ ወደ ስሬዶሮ ከተማ በመጓዝ ላይ ሳሉ እንደኾነ መስማቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ጥቃቱን ያደረሱት የፋኖ ታጣቂዎች ናቸው በማለት የአካባቢው ምንጮች መናገራቸውን ጠቅሷል። 4፤ ብሄራዊ ባንክ፣ "ሰን ፔይ ሶሊዩሽን" የተሰኘውን የፋይናንስ አስተዳደር እና ክፍያ ሥርዓት አገልግሎት ሰጪ ኩባንያ ፍቃድ እንደሠረዘ ሸጋ ሜዲያ ዘግቧል። ኩባንያው ከሁለት ዓመት በፊት የፋይናንስ ክፍያ አገልግሎት ለመስጠት ከባንኩ ፍቃድ ወስዶ ነበር። ባንኩ የኩባንያውን ፍቃድ የሠረዘው፣ ኩባንያው ሥራ አስፈጻሚ መሾም አለመቻሉን፣ የንግድ ፍቃዱን አለማሳደሱንና የአክሲዮን ባለድርሻዎች ስብሰባ ማካሄድ አለመቻሉን በመጥቀስ እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። የኩባንያውን ከፍተኛ ድርሻ የያዘው፣ የታዋቂው የሪል እስቴትና ኮንስትራክሽን ኢንቨስትመንት ባለሃብት የሳሙዔል ታፈሠ ልጅ ዮናስ ሳሙዔል እንደኾነ ዘገባው ጠቅሷል። 5፤ ቱርክ፣ በሱማሊያ ባሕር ዳርቻ የተፈጥሮ ጋዝ ፍለጋ ለመጀመር አንዲት መርከብ በቀጣዩ ወር ወደ ሱማሊያ የባሕር ዳርቻ ልትልክ መኾኗን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ቱርክ፣ የተፈጥሮ ጋዝ ፈላጊ መርከቧን ደኅንነት የሚጠብቁ ቢያንስ ሁለት የባሕር ኃይል መርከቦችን ጭምር በሱማሊያ የውቅያኖስ ጠረፍ ለማሠማራት እንዳቀደች ዘገባዎቹ አመልክተዋል። ቱርክ፣ እያንዳንዳቸው አምስት ሺሕ ስኩዌር ኪሎ ሜትር ስፋት ባላቸው ሦስት ቦታዎች ላይ የጋዝ ፍለጋ እንድትጀምር ከሱማሊያ ፍቃድ ማግኘቷን ገልጣለች። ቱርክና ሱማሊያ ባለፈው መጋቢት የጋዝ ክፍፍል ስምምነት ተፈራርመዋል። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
ለቸኮለ! ረቡዕ መስከረም 8/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ ኢጋድ፣ ኢትዮጵያና ሶማሊያ በባሕር በር ውዝግብ ዙሪያ የገቡበትን ውጥረት በድርድር ለመፍታት ጥረት እንደጀመሩ ከምንጮች መስማቱን ጠቅሶ ሪፖርተር ዘግቧል። ኢጋድ ሁለቱ አገሮች ውጥረቱን በውይይት እንዲፈቱ ለማስቻል ከተጀመረው ጥረት ጀርባ፣ የጂቡቲ፣ የኬንያና የአሜሪካ መንግሥታት ድጋፍ እንዳለ ምንጮች መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል። የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ ሰሞኑን ወደ ሞቃዲሾ አቅንተው ከሶማሊያ ባለሥልጣናት ጋር በቀጠናዊ ጉዳዮች ዙሪያ መምከራቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያ ከሴማሌላንድ ጋር በተፈራረመችው የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት ሳቢያ በሁለቱ አገራት መካከል የተፈጠረውን ውዝግብ በድርድር ለመፍታት ኢጋድ አዲስ ጥረት የጀመረው፣ በቱርክ አሸማጋይነት የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚንስትሮች አንካራ ውስጥ በሁለት ዙሮች ያደረጓቸው ቀጥተኛ ያልኾኑ ንግግሮች ውጤት ሳያስገኙ መቅረታቸውን ተከትሎ ነው። ትናንት አንካራ ውስጥ ሦስተኛው ዙር ንግግር ይጀመራል ተብሎ ተጠብቆ የነበረ ቢኾንም፣ ቱርክ በይፋ ባልገለጠችው ምክንያት ንግግሩ ሳይጀመር ቀርቷል። 2፤ በሰሜን ጎንደር ዞን በደባርቅ እና ዳባት ከተሞ በመንግሥት ኃይሎችና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በተካሄደው ውጊያ ዘጠኝ ሰዎች እንደተገደሉ መስማቱን ጠቅሶ እንግሊዝኛው ቪኦኤ ጣቢያ ዘግቧል። ደባርቅ ሆስፒታል ብቻ ሕጻናትንና ተዋጊዎችን ጨምሮ 30 ያህል ሰዎች ቁስለኞችን ማከሙን እንደተናገረ ዘገባው አመልክቷል። በውጊያው ሳቢያ በሁለቱ ከተሞች የንግድ መደብሮችና የመንግሥት ቢሮዎች ሰኞ እና ማክሰኞ'ለት ተዘግተው እንደዋሉ ተገልጧል። በጎንደሩ ውጊያ በትንሹ አምስት ሰዎች መገደላቸውን ከነዋሪዎች መስማቱን ጠቅሶ የዘገበው ደሞ ዶቸቨለ ነው። አዘዞ አካባቢ በተደረገ የተኩስ ልውውጥ ሦስት ሰዎች እንዲኹም ቡልኮ በተባለ አካባቢ በከባድ መሳሪያ ተኩስ ሁለት ሕጻናት መገደላቸውን ነዋሪዎች መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። 3፤ ኦብነግ፣ በኢትዮጵያና ሱማሊያ መካከል በተፈጠረው ውጥረት ሳቢያ የሶማሌ ክልል ሕዝብ ተጎጂ መኾን የለበትም ሲል ዛሬ ባወጣው መግለጫ አሳስቧል። በሶማሌ ክልል ባሁኑ ወቅት ወታደራዊ እንቅስቃሴ ተበራክቷል ያለው ኦብነግ፣ ክልሉ "በወታደራዊ አስተዳደር ሥር" ሊወድቅ እንደሚችልና ይህም የሶማሌ ሕዝብን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት እንደሚሸረሽር ገልጧል። ኦብነግ፣ ፌደራል መንግሥቱ በሶማሌ ክልል ውስጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚፈጽማቸው ድርጊቶች በሕገመንግሥቱ በአንቀጽ 39 የተደነገገውን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት የሚጥሱ ናቸው በማለትም ከሷል።  4፤ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ፣ ፌደራል መንግሥቱ የትግራይ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው እንዳይመለሱ ያገዱ እንቅፋቶችን እንዲቀርፍ ዛሬ በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክን መቀሌ ውስጥ ባነጋገሩበት ወቅት ባደረጉት ንግግር ጠይቀዋል። ጌታቸው የኤርትራ ሠራዊት በምሥራቃዊ ትግራይ በተለይ በኢሮብ ወረዳ እስካሁን መኖሩ፣ በኢሮብ ብሄረሰብ ሕልውና ላይ አደጋ ደቅኗል ማለታቸውንም የክልሉ ቴሌቪዥን ዘግቧል። ተዋጊዎችን ትጥቅ የማስፈታት፣ የመበተንና መልሶ የማዋሃድ ጉዳይ፣ መሬት ላይ ባለው የጸጥታ ኹኔታ ሊወሰን ይገባዋል በማለት ጌታቸው እንዳሳሰቡ ዘገባው አመልክቷል። አምባሳደር ላሜክ፣ የፕሪቶሪያው የግጭት ማቆም ስምምነት ባግባቡ ሊተገበር እንደሚገባው አሳስበዋል ተብሏል። 5፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ከ2013 ዓ፣ም እስከ ጥር 2016 ዓ፣ም ባሉት ዓመታት 144 የድሮን ጥቃቶች እንደተተፈጸሙ ማረጋገጡን ቢቢሲ ዘግቧል። የፖለቲካ ግጭቶችንና ተቃውሞዎችን የሚመዘግበው "አርምድ ኮንፍሊክት ሎኬሽን ኤንድ ኤቨንት ዳታ" (አክሌድ) የተባለው ዓለማቀፍ ተቋም፣ በአማራ ክልል እስከ ጥር 2016 ዓ፣ም ድረስ 49 የድሮን ጥቃቶች እንደተፈጸሙ መመዝገቡን ዘገባው ጠቅሷል። በኦሮሚያ ክልል ደሞ 28 የድሮን ጥቃቶች እንደተፈጸሙ የአክሌድ መረጃ እንደሚያሳይ ዘገባው አመልክቷል። በአክሌድ መረጃ መሠረት፣ ከታኅሳስ 2013 ዓ፣ም እስከ የካቲት 2016 ዓ፣ም ባሉት ጊዜያት 139 የተረጋገጡ የድሮን ጥቃቶች እንደተፈጸሙ እንደሚያመለክት ተገልጧል። መንግሥት፣ በድሮን ጥቃት "ጽንፈኛ ኃይሎችን' እንጂ ሰላማዊ ሰዎችን ዒላማ አላደረኩም በማለት ቀደም ሲል ማስተባበሉ አይዘነጋም። 6፤ ለበርካታ ወራት በእስር ላይ የቆዩት የበይነ መረብ ጋዜጠኞቹ በላይ ማናዬ እና በቃሉ አላምረው ባለፈው ሳምንት ከአገር መሰደዳቸው ተሰምቷል። ጋዜጠኞቹ የመሰደድ የተገደዱት፣ የመንግሥት የጸጥታ አባላት “ለሕይወታቸው የሚያሰጋ" ማስጠንቀቂያ እንደሰጧቸው እና "ክትትል" እንደሚያደርጉባቸው በመግለጽ እንደኾነ የአገር ውስጥ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። በአማራ ክልል ታውጆ ከነበረው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋር በተያያዘ ለእስር የተዳረጉት በላይ እና በቃሉ፣ ከእስር የተፈቱት ከሦስት ወራት በፊት ነበር። "አልፋ ሚዲያ” የተሰኘ የበይነ መረብ ጣቢያ መስራችና አዘጋጅ የኾነው በቃሉ ለዘጠኝ ወራት አዋሽ አርባ ወታደራዊ ማሠልጠኛ ውስጥ ታስሮ የነበረ ሲኾን፣ የ"ኢትዮ ኒውስ” የበይነ መረብ ጣቢያ መስራችና አዘጋጅ በላይም በተመሳሳይ ቦታ ለሰባት ወራት እንደታሠረ ይታወሳል። 7፤ የቦሮ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግሥት አመራሮች በሕዝቡ ላይ ለምን የቦሮ ፓርቲን ዕጩዎች በሰኔው ምርጫ መረጣችሁ በማለት ዛቻና ማስፈራሪያ ሰንዝረዋል በማለት ከሷል። ፓርቲው፣ የክልሉ መንግሥት ለዚህ ድርጊት ሕዝቡን ባስቸኳይ ይቅርታ እንዲጠይቅ አሳስቧል። በአመራሮቹ፣ በአባላቱና ደጋፊዎቹ ላይ እስራትና ድብደባ እንደሚፈጸምባቸውና በሕገወጥ መንገድ ከሥራ እንደሚዛወሩ የገለጠው ፓርቲው፣ የክልሉ መንግሥት አካሄዱን እንዲያርም አሳስቧል፡፡ የክልሉ መንግሥት ድርጊቶቹን ካላረመ፣ ከመንግሥት ጋር አብሮ ለመስራት ያሳለፈውን ውሳኔ በድጋሚ ለማጤን እንደሚገደድ ፓርቲው አስጠንቅቋል። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 2
ለቸኮለ ማለዳ! ማክሰኞ መስከረም 7/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ የኤርትራ ሠራዊት በድንበር አካባቢ የሚገኙ በርከት ያሉ ቦታዎችን አኹንም እንደተቆጣጠረ መኾኑን ዋዜማ ከአካባቢው ነዋሪዎችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ካገኘችው መረጃ ተረድታለች። በትግራይ ምሥራቃዊ ዞን ኢሮብ ወረዳ ኹለት ቀበሌዎች ሙሉ በሙሉና ሌሎች ኹለት ቀበሌዎች በከፊል በኤርትራ ይዞታ ሥር እንደሚገኙና የባንክ፣ ስልክና ትራንስፖርት አገልግሎቶች እንደተቋረጡ መኾኑ ታውቋል። በአራቱም ቀበሌዎች፣ 16 ሺሕ ሕዝብ የጤና አገልግሎት እንደማያገኝ ዋዜማ ሰምታለች። በኤርትራ ሥር ለመተዳደር ፍቃደኛ እንዲኾኑ ወይም አካባቢውን እንዲለቁ ምርጫ ከቀረበላቸው የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል፣ ወደ አዲግራት የመጡ መኖራቸውንም ምንጮች ተናግረዋል። የዛላንበሳ ከተማም ሙሉ በሙሉ በኤርትራ ቁጥጥር ሥር ስትኾን፣ ከከተማዋ የተፈናቀሉ ነዋሪዎቿም ነጻ በኾነው ጉሎመሃዳ ወረዳ ውስጥ ተጠልለዋል ተብሏል። 2፤ ሕወሓት፣ ምክትል ሊቀመንበሩን ጌታቸው ረዳን ጨምሮ 16 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቱን ማባረሩንና ከድርጅታዊ ሃላፊነታቸውና በጊዜያዊ አስተዳደሩ ካላቸው ውክልና በሙሉ ማንሳቱን ትናንት ምሽት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። ማዕከላዊ ኮሚቴው አሰናብቻቸዋለሁ ያላቸውን አባላቱን በሙስና ወንጀል ጭምር እንደሚጠይቃቸው ገልጧል። ማዕከላዊ ኮሚቴው ከፓርቲ አባልነት አባርሬያቸዋለሁ ያላቸው፣ ጌታቸው ረዳ፣ በየነ ምክሩ፣ ፕሮፌሰር ክንደያ ገ/ሂወት፣ ሓጎስ ጎዲፈይ፣ ኣልማዝ ገ/ጻዲቅ፣ ረዳኢ ሓለፎም፣ ሰብለ ካሕሳይ፣ ኢሳያስ ታደሠ፣ ሰለሞን መዓሾ፣ ሺሻይ መረሳ፣ ገብረሂወት ገብረእግዜር፣ ርስቁ አለማው፣ ሃፍቱ ኪሮስ፣ ብርሃነ ገ/እየሱስ፣ ሩፋኤል ሽፋረ እና ነጋ አሠፋ ናቸው። የምርጫ ቦርድ እውቅና የሌለው ቢኾንም፣ የፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔ በስም የተጠቀሱትን ግለሰቦች ከማዕክላዊ ኮሚቴ ቀደም ሲል ማገዱ ይታወሳል። 3፤ ግብጽ፣ ኤርትራን ከሕወሓት ጋር ለማስታረቅ በምትችልበት ኹኔታ ዙሪያ ከኤርትራ ጋር እየመከረች መኾኗን የኢምሬቶች ጋዜጣ ናሽናል ዘግቧል። ኤርትራ እና ግብጽ የወታደራዊ ትብብርና የመረጃ ልውውጥ ለማድረግ አማራጮችን እየፈተሹ እንደኾነም ዘገባው ጠቅሷል። ሁለቱ አገራት ለመፈራረም ያስቡት ስምምነት፣ በቀይ ባሕር አካባቢ የመርከቦችን ደኅንነት ለማረጋገጥ ርምጃዎችን መውሰድን ያካትታል ተብሏል። የግብጽ ደኅንነት ሚንስትር ጀኔራል ከማል አባስና ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ባድር አብደላቲ ሰሞኑን አሥመራ ውስጥ ከፕሬዝዳንት ኢሳያስ ጋር መወያየታቸው ይታወሳል። 4፤ ትሬድ ማርክ አፍሪካ የተሰኘው አሕጉራዊ ድርጅት፣ የኢትዮጵያን የቀድሞ ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን የቦርድ ሊቀመንበሩ አድርጎ ሰሞኑን ሾሟል። ኃይለማርያም የድርጅቱ የቦርድ ሊቀመንበር ኾነው የተሾሙት፣ ለቀጣዮቹ ስምንት ዓመታት ነው። ትሬድ ማርክ አፍሪካ፣ በአፍሪካ አገራት መካከል፣ የንግድ ልውውጥና የወጪ ንግድ እንዲጨምር የሚሠራ ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት ነው። ኃይለማርያም ድርጅቱን በቦርድ ሊቀመንበርነት የተቀላቀሉት፣ ድርጅቱ በአገራት መካከል የሚደረግ የሸቀጦች ዝውውር የሚፈጀውን ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ለመቀነስ ስትራቴጂክ ግብ በያዘበት ወቅት ላይ ነው። 5፤ የሱዳኑ ወታደራዊ መሪ ጀኔራል ቡርሃን፣ ከደቡብ ሱዳን ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር ጋር ለመነጋገር ትናንት ጁባ ገብተዋል። ጀኔራል ቡርሃንና ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር በቀጠናዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚነጋገሩ የጁባ ባለሥልጣናት ገልጸዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች ደቡብ ሱዳን ውስጥ ቅጥረኛ ተዋጊዎችን ይመለምላሉ የሚል ጥርጣሬ እንዳለው ተመድ ገልጧል። ደቡብ ሱዳን፣ በሱዳኗ ፓርት ሱዳን በኩል የምታስወጣው ነዳጅ በጦርነቱ ሳቢያ ከተስተጓጎለ በርካታ ወራት ተቆጥረዋል። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
ለቸኮለ! ማክሰኞ መስከረም 7/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ በጎንደር ከተማና አካባቢዋ በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ከትናንት ሌሊት ጀምሮ እስከ ዛሬ እኩለ ቀን ድረስ ውጊያ ሲካሄድ እንደነበር የአገር ውስጥ የዜና ምንጮች ዘግበዋል። ዛሬ አዘዞ፣ ቀበሌ 18፣ አዲስ ዓለም፣ አይራ እና ዓለም በር በተባሉ የከተማዋ አካባቢዎች፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል ከፍተኛ የተኩስ ልውውጥ ሲደረግ መዋሉን ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። በውጊያው በርካታ ሰላማዊ ሰዎች እንደተገደሉና እንደቆሰሉም ዘገባዎቹ አመልክተዋል። በተመሳሳይ፣ በሰሜን ጎንደር ዞን መቀመጫ ደባርቅ፣ በዳባት ወረዳ በዳባት እና በወገራ ወረዳ በአምባ ጊዮርጊስ ከተሞች፣ ዛሬን ጨምሮ ሰሞኑን ውጊያ ሲደረግ መሰንበቱና ቁጥራቸው ያልታወቀ ሲቪሎች መገደላቸው ተዘግቧል። 2፤ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ ከቦሌ ወደ መቀሌ ሊበር በነበረ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ውስጥ ሁከት በመፍጠር ክስ የተመሠረተባቸው ስድስት ተከሳሾች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ማድረጉን የአገር ውስጥ ዜና አውታሮች ዘግበዋል። ዓቃቤ ሕግ በግለሰቦቹ ላይ የመሠረታቸው ክሶች፣ ከአውሮፕላን አንወርድም በማለት አውሮፕላኑን ያለአግባብ የመያዝ ወንጀል፣ የመንግሥት ሠራተኛ የሥራ ግዴታውን እንዳይወጣ ማስተጓጎልና አለመታዘዝ የሚሉ ናቸው፡፡ አንደኛ ተከሳሽ ዮሃንስ ዳንዔል፣ የአየር መንገዱን መልካም ስም በሚያጎድፍ መልኩ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን በኮምፒውተር ሥርዓት አማካኝነት አሠራጭቷል የሚል ክስ ጭምር እንደተመሠረተበት ይታወሳል። ተከሳሾቹ የተጠረጠሩባቸው ወንጀሎች ተደራራቢ መኾናቸውን ጠቅሶ የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ ያደረገው ፍርድ ቤቱ፣ ክሱን ጥቅምት 4 ለመመልከት ቀጠሮ እንደሰጠ ተገልጧል። 3፤ ፖለቲከኛ፣ የዩኒቨርሲቲ መምህር እና ተመራማሪ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ በሕክምና ሲረዱ ከቆዩ በኋላ በ74 ዓመታቸው ዛሬ ጧት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ፕሮፌሰር በየነ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለበርካታ ዓመታት በባዮሎጂ አስተማሪነትና በባዮሎጂ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበርነት ያገለገሉ ሲኾን፣ በዘርፉ በርካታ የምርምር ሥራዎችን እንደሠሩ ይነገርላቸዋል። ፕሮፌሰር በየነ፣ በሽግግር መንግሥቱ ዘመን ምክትል የትምህርት ሚንስትር ኾነውም አገልግለዋል። በፖለቲካው ዓለም የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ኅብረትን እና "መድረክ" የተባለውን የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት ለዓመታት የመሩት ፕሮፌሰር በየነ፣ እስከ'ለተ ሞታቸው ድረስ የኢትዮጵያ ሶሻል ዲሞክራሲያዊ ፓርቲን በሊቀመንበርነት የመሩና ለዓመታት በሽግግር መንግሥቱ ምክር ቤትና በፌደራሉ ፓርላማ አባል የነበሩ ናቸው። ፕሮፌሰር በየነ፣ እስከ ሕልፈታቸው ድረስ የመንግሥታዊው ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ነበሩ። 4፤ የብር ምንዛሬ ከዶላርና ሌሎች የውጭ ምንዛሬዎች አንጻር በዛሬው ዕለት በከፍተኛ ደረጃ መዳከሙን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የምንዛሬ መረጃ አመልክቷል። ንግድ ባንክ ዛሬ አንድ ዶላር እየገዛበት ያለው ዋጋ፣ ወደ 112 ብር ከ39 ሳንቲም ያሻቀበ ሲኾን፣ የመሸጫ ዋጋው ደሞ ወደ 124 ብር ከ75 ሳንቲም ከፍ ብሏል። ባንኩ አንድን ዶላር ዛሬ የሚገዛበት ዋጋ ከትናንቱ ጋር ሲነጻጸር ከ4 ብር በላይ ጭማሪ ያሳየ ሲኾን፣ መሸጫው ደሞ 5 ብር ጭማሪ አሳይቷል። አንድ ፓውንድ ዛሬ በ141 ብር ከ63 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ157 ብር ከ94 ሳንቲም እየተሸጠ እንደሚገኝም ባንኩ ገልጧል። በተመሳሳይ፣ አንድ ዩሮ በ125 ብር ከ01 ሳንቲም እየተገዛ፣ በ138 ብር ከ76 ሳንቲም እየተሸጠ ይገኛል። 5፤ ደቡብ ሱዳን፣ ነዳጇን በፖርት ሱዳን በኩል ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንድትቀጥል ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር እና ጀኔራል አብዱልፈታህ አል ቡርሃን ዛሬ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል። የነዳጅ ማስተላለፊያ ቧንቧው በሱዳኑ ጦርነት ጉዳት ደርሶበት፣ ደቡብ ሱዳን ላለፉት አራት ወራት ነዳጅ ለውጭ ገበያ ማቅረብ አልቻለችም። ከፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር ጋር ለመወየት ትናንት ጁባ የገቡት ጀኔራል ቡርሃን፣ በነዳጅ ማስተላለፊያው ቧንቧ ላይ ሲደረግ የነበረው ጥገና ተጠናቋል በማለት ተናግረዋል። ሁለቱ መሪዎች ይህን ይበሉ እንጂ፣ ከፊሉ ቧንቧ የሚያልፈው የሱዳን ፈጥኖ ደራሹ ኃይል በሚቆጣጠራቸው አካባቢዎች እንደኾነ ይታወቃል። 6፤ ሜታ ኩባንያ፣ የሩሲያውን ቴሌቪዥን ጣቢያ "አር ቲ" "ሐሰተኛ መረጃ በማሠራጨት ያልተገባ ተጽዕኖ" ለመፍጠር ሲሞክር ቆይቷል በማለት ከፌስቡክ፣ ኢንስታግራምና ዋትስአፕ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች አግዶታል። አሜሪካ፣ በሩሲያ መንግሥት ቁጥጥር ሥር የሚገኘው "አር ቲ" ለአንድ ተቋም 10 ሚሊዮን ዶላር ከፍሎ የሩሲያ መንግሥትን ድብቅ መልዕክቶች ለማስተላለፍ ሞክሯል፤ ጣቢያው የሩሲያ ስለላ ተቋም አካል ኾኗል በማለት ክስ አሰምታ ነበር። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 3 3
ለቸኮለ! ሰኞ መስከረም 6/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ መንግሥትን እና የፋኖ ታጣቂዎችን ወደ ድርድር ለማምጣት የማመቻቸት ጥረት እያደረገ የሚገኘው በአማራ ክልል የተቋቋመው የሰላም ምክር ቤት፣ ዛሬ በአዲስ አበባ የካናዳ አምባሳደር ጆሿ ታባህ ጋር ተወያይቷል። ውይይቱ ሁለቱን ወገኖች ወደ ድርድር እንዲመጡ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰቡ ጫና እንዲፈጦር ምክር ቤቱ የጀመረው ጥረት አካል ነው። አምባሳደሩ፣ ካናዳ የአማራ ክልልን ሁኔታ በንቃት እንደምትከታተል በመግለጽ፣ የምክር ቤቱን ጥረት እንደሚደግፉ ገለጸዋል። 2፤ በትግራይ ክልል የሚንቀሳቀሱ አራት ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ በክልሉ ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች በእኩልነት የሚሳተፉበት አዲስ ሲቪል ጊዜያዊ አስተዳደር እንዲቋቋም ጠይቀዋል። በክልሉ ባሁኑ ወቅት የተፈጠረው ችግር ፖለቲካዊ መኾኑን የገለጡት ፓርቲዎቹ፣ ችግሩ ሊፈታ የሚችለው ምክር ቤት ያለው ሁሉን አካታች ጊዜያዊ አስተዳደር ሲቋቋም ብቻ እንደኾነ ገልጸዋል። ይህንኑ ጥሪ ዛሬ ያቀረቡት፣ ባይቶና፣ ሳልሳይ ወያነ ትግራይ፣ ውድብ ናጽነት ትግራይ እና አረና፣ የክልሉ ጸጥታ ሃይሎች በፖለቲካዊ ወገንተኝነት ነጻ በመኾን በአዲሱ ሲቪል አስተዳደር ሥር በሕግ የሚመሩ እንዲኾኑ ጠይቀዋል። የትግራይ ፖለቲከኞች ተፈናቃዮችን ወደ ቀያቸው በመመለስ፣ የክልሉን ሕገመንግሥታዊ ወሰን በማስመለስ እንዲሁም የቀድሞ ተዋጊዎችን ትጥቅ በማስፈታት፣ በመበተን እና መልሶ በማዋሃድ ዙሪያ ከፌደራል መንግሥቱ ጋር የደረሱባቸውን ስምምነቶች ለሕዝብ ግልጽ እንዲያደርጉና የስምምነቶቹን የእስካኹን አፈጻጸም ይፋ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። 3፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ ከመስከረም ወር ጀምሮ በመጪዎቹ ሦስት ወራት የኤሌክትሪክ አገልግሎት በኪሎ ዋት እስከ 95 ብር ድረስ ጭማሪ እንደሚደረግበት አስታውቋል። ከተያዘው ዓመት ጀምሮ በሚደረገው የኤሌክትሪክ ፍጆታ ታሪፍ ማሻሻያ መሠረት፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ክፍያ እስከ 40 በመቶ ጭማሪ ይደረግበታል፡፡ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚዎች የማመንጫ ታሪፍ ላይ ቀደሞ ይከፍሉት ከነበረው ሂሳብ በኪሎ ዋት የ42 ሳንቲም ጭማሪ እንደሚደረግ የተቋሙ መረጃ ያሳያል፡፡ ባንጻሩ፣ ከፍተኛ የኃይል ተጠቃሚ የኾኑ ደንበኞች የማመንጫ ታሪፍ በኪሎ ዋት የ81 ሳንቲም ይጨመርባቸዋል። በተመሳሳይ፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ለኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ ከዚህ ቀደም ይከፍሉት ከነበረው ታሪፍ ላይ በኪሎ ዋት 26 ብር ከ34 ሳንቲም ጭማሪ ይከፍላሉ። በከፍተኛ የኃይል ተጠቃሚዎች ላይ ደሞ፣ ቀድሞ ይከፍሉት ከነበረው የኃይል ማስተላለፊያ ታሪፍ ይከፍሉት ከነበረው በኪሎ ዋት 95 ብር ከ87 ሳንቲም ጭማሪ ተደርጓል። 4፤ ኢዜማ፣ ገዢው ብልጽግና ፖርቲ የመንግሥት እና የፓርቲ ሥራዎችን መቀላቀልን በማናለብኝነት መንገድ ገፍቶበታል በማለት ዛሬ ባወጣው መግለጫ ከሷል፡፡ ኢዜማ፣ ገዥው ፓርቲ ሰሞኑን ለአባሎቹ ሥልጠና የተጠቀመበትን ሃብትና ንብረት ወደ መንግሥት ካዝና እንዲመለስም ጠይቋል። ዲሞክራሲያዊ ተቋማትም፣ መንግሥትን ተጠያቂ እንዲያደርጉና የአገሪቱን ሃብት ከሙስና እና ምዝበራ እንዲታደጉ አሳስቧል። ገዥው ፓርቲ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ላይ አደጋ እና ስጋት የሚደቅኑ ተግባራትን በተደጋጋሚ በመሥራት ለተጠያቂነት ዝግጁ አለመኾኑን እያሳየ ይገኛል ያለው ኢዜማ፣ ይህ አካሄድ የሚያመጣው መዘዝ ቀላል አለመኾኑ ሊታወቅ ይገባል በማለት አስጠንቅቋል፡፡ ኢዜማ፣ ገዥው ፓርቲ ስህተቱን በማረም የመንግሥትን ሃብትና ንብረት እንዳይባክን እና የመንግሥት መገናኛ ብዙሃንም በገለልተኛነት ይህን ተግባር እንዲያወግዙ አሳስቧል። 5፤ ሱዳን ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ የትግራይ ተወላጅ ስደተኞች ያሉበትን አስከፊ ኹኔታ በማስመልከት ሰላማዊ ሰልፍ ማድረጋቸውን የትግራይ ቴሌቪዥን ዘግቧል። ስደተኞቹ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት፣ ባስቸኳይ ወደ አገራቸው እንዲመልሷቸው ጥያቄ ማቅረባቸውን ዘገባው አመልክቷል። በጦርነት በምትታመሰው ሱዳን፣ ባሁኑ ወቅት ችግራቸውን የሚፈታላቸው አካል ማግኘት እንዳልቻሉም ስደተኞቹ በሰላማዊ ሰልፉ ላይ ገልጸዋል ተብሏል። በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ከሑመራ እና ወልቃይት አካባቢዎች ወደ ሱዳን የተሰደዱት፣ የሰሜኑ ጦርነት መቀስቀሱን ተከትሎ ነበር። የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ፣ የሱዳኑ ጦርነት ስደተኞቹ ወደሚገኙበት መጠለያ መቃረቡን በመግለጽ፣ ፌደራል መንግሥቱ የትግራይ ተወላጅ ስደተኞች ከሱዳን ወደ አገራቸው የሚመለሱበትን ኹኔታ እንዲያመቻች ከጥቂት ሳምንታት በፊት መጠየቃቸው አይዘነጋም። 6፤ የኢጋድ ዋና ጸሃፊ ወርቅነህ ገበየሁ፣ ዛሬ ሞቃዲሾ ውስጥ ከሱማሊያ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሕመድ ፊቂ ጋር በቀጠናዊ ሰላም እና ጸጥታ ዙሪያ መነጋገራቸውን አስታውቀዋል። የሱማሊያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሕመድ ፊቂም፣ የሱማሊያ መንግሥት ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር እንጂ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ጠብ እንደሌለው መግለጣቸውን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ወርቅነህ ወደ ሞቃዲሾ ያቀኑት፣ ፊቂ ኢትዮጵያ ከሶማሌላንድ ጋር የተፈራረመችውን የባሕር በር ስምምነት ተግባራዊ ካደረገች፣ ሱማሊያ ለኢትዮጵያ አማጺ ኃይሎች ጦር መሳሪያ ልታስታጥቅ ትችላለች በማለት በተናገሩ ማግስት ነው። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 8
ለቸኮለ! ቅዳሜ መስከረም 4/2017 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ በኢትዮጵያ ለሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦት ሥራው የአገሪቱ የጸጥታ ኹኔታ ትልቅ እንቅፋት እየፈጠረበት መኾኑን መናገሩን ዘ ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል። በአማራ፣ ኦሮሚያ፣ ጋምቤላ፣ ሱማሌ፣ አፋር እና በከፊል ትግራይ ክልሎች የጸጥታ ችግሮች በዕርዳታ ሥርጭቱና በረድዔት ሠራተኞቹ ደኅንነት ላይ ስጋት እንደደቀነ ድርጅቱ መግለጡን ዘገባው ጠቅሷል። የድርጅቱ ካሚዮኖች የጫኑትን ሰብዓዊ ዕርዳታ ታጣቂዎች በተደጋጋሚ አስገድደው እንደወሰዱትና በዚህም ሳቢያ ዓለማቀፍ ለጋሾች ጥያቄ እያነሱበት መኾኑን ተናግሯል ተብሏል። ድርጅቱ በኢትዮጵያ የዕርዳታ ሥራውን ለመቀጠል በቅርቡ 30 ሚሊዮን ዶላር ባይበደር ኖሮ፣ በተያዘው ወር የዕርዳታ ክምችቱ ሙሉ በሙሉ ይሟጠጥ እንደነበርም በዘገባው ላይ ተገልጧል። 2፤ ራስ ገዙ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቅድመ-ምረቃ የፍልስፍና እና የትግርኛ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ትምህርት ፕሮግራሞቹን ዘንድሮ እንደሚዘጋ መስማቱን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል። ዩኒቨርሲቲው ሁለቱን የትምህርት ክፍሎች ለመዝጋት የወሰነው፣ በተማሪ እጥረት ሳቢያ ትምህርት ክፍሎቹ ለተከታታይ ዓመታት አዲስ የቅድመ-ምረቃ ተማሪዎችን ባለመቀበላቸው እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። የፍልስፍና ትምህርት ክፍል ላለፉት ስድስት ዓመታት እንዲሁም ትግርኛ ቋንቋ ለአምስት ዓመታት አዲስ የቅድመ ምረቃ ተማሪዎችን አልተቀበሉም ተብሏል። ከሐምሌ ጀምሮ ራስ ገዝ የኾነው ዩኒቨርሲቲው፣ ከዘንድሮ ጀምሮ ከሚተገብረው አዲሱ የተማሪ ቅበላ ፖሊሲው ጋር በሚጣጣም መልኩ በርካታ የትምህርት ክፍሎችን እንደገና በማዋቀር ላይ ይገኛል። 3፤ የሱማሊያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሕመድ ፊቂ፣ ኢትዮጵያ ከሶማሌላንድ ጋር የተፈራረመችውን የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት የምትተገብር ከኾነ፣ "ሱማሊያ የኢትዮጵያ መንግሥትን ለመጣል የሚዋጉ አማጺ ኃይሎችን ጦር መሳሪያ ልታስታጥቅ ትችላለች" በማለት ዩኒቨርሳል ለተባለ የሱማሊኛ ቴሌቪዥን ጣቢያ መናገራቸውን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ፊቂ፣ እስካኹን ያለው ኹኔታ ግን ሱማሊያ ያን አማራጭ እንድትከተል የሚያደርግ ደረጃ ላይ አልደረሰም ማለታቸውንም ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ መበታተን የሱማሊያም ኾነ የአፍሪካ ቀንድ ቀጠና ፍላጎት እንዳልኾነም ፊቂ መናገራቸውን ዘገባዎቹ አመልክተዋል። በተያያዘ፣ ሱማሊያ ከግብጽ ተጨማሪ የጦር መሳሪያ ድጋፍ በቅርቡ ታገኛለች ሲሉ ባለሥልጣናቷ ተናግረዋል። 4፤ በአፍሪካ ኅብረት የኢትዮጵያ ምክትል ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ነቢዩ ተድላ፣ "የአልሸባብ ወኪሎች" የሱማሊያ መንግሥት ባለሥልጣናት ኾነው መቅረባቸው "አስቂኝ ነገር" ነው በማለት የሱማሊያ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሕመድ ፊቂ የኢትዮጵያን አማጺ ኃይሎች ልናስታጥቅ እንችላለን በማለት የሰጡትን አስተያየት ተችተዋል። አምባሳደር ነቢዩ ዛሬ በ"ኤክስ" ገጻቸው ላይ ባሠፈሩት አስተያየት፣ ከሞቃዲሾና አካባቢዋ ውጭ ማስተዳደር የማይችሉት የሱማሊያ ባለሥልጣናት፣ "ለጠባብ" የጎሳ ፍላጎታቸው ሲሉ "ባዶ ብሄርተኝነትን" በመስበክ ላይ እንደኾኑ ገልጸዋል። እንዲህ ያለው አካሄድ፣ ለዓመታት የተገኙ "መሻሻሎችን የሚቀለብስ" እና "ሱማሊያን አዘቅጥ ውስጥ የሚከት" እንደኾነም አምባሳደር ነቢዩ ጠቁመዋል። 5፤ የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ እና የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ባድር አብደላቲ ዛሬ አሥመራ ውስጥ ባደረጉት ውይይት፣ ግብጽ በአፍሪካ ቀንድ ቀጠና "አለመረጋጋት የመፍጠርና የጣልቃገብነት አጀንዳ ታራምዳለች" በማለት አንዳንድ አካላት የሚያቀርቡት ውንጀላ "መሠረተ ቢስ" እና "ለስትራተጂካዊ ስህተታቸው ማሳመኛነት የሚያሰሙት ባዶ ውንጀላ" ነው የሚል የጋራ ግንዛቤ እንደያዙ ተሰምቷል። ሁለቱ ወገኖች በሁለትዮሽና የሱማሊያና ሱዳን ወቅታዊ ኹኔታዎችን ጨምሮ በቀጠናዊ ጉዳዮችና በቀይ ባሕር ላይ በሚከሰቱ የጸጥታ ስጋቶች ዙሪያ "ሰፋ ያለ ውይይት" ማድረጋቸውን የኤርትራ መንግሥት ቃል አቀባይ የማነ ገ/መስቀል ገልጸዋል። የሁለቱ አገራት ትብብር ለቀጠናዊ ሰላምና መረጋጋት መሠረት ነው ያሉት ሁለቱ ወገኖች፣ በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ንግድ፣ ግብርናና ጤና ትብብራቸውን ለማሳደግ እንደተስማሙም የማነ ገልጸዋል። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 7
ለቸኮለ ማለዳ! ቅዳሜ መስከረም 4/2016 ዓ፣ም የዋዜማ ዕለታዊ ዜናዎች 1፤ በአፋሮችና ሶማሌዎች መካከል ሲካሄድ የቆየው የጎሳ ግጭት እንደቆመ ለግጭቱ መፍትሄ ለመስጠት የተቋቋመው ብሄራዊ ኮሚቴ መግለጡን ፋና ብሮድካስት ዘግቧል። ብሄራዊ ኮሚቴው፣ በግጭት አካባቢዎች በመከላከያና ፌደራል ፖሊስ ቁጥጥር ሥር የኾነ ነጻ ቀጠና እንደተቋቋመና ግጭቶችን ማስቆ እንደተቻለ ኮሚቴው መናገሩን ዘገባው አመልክቷል። የሰላም ሚንስትር ብናልፍ አንዷለም፣ ከነጻ ቀጣናው ያልወጡ ቀሪ ታጣቂ ኃይሎች ባስቸኳይ እንዲወጡ ማድረግና በአወዛጋቢ አካባቢዎች ሠፈራዎችን ማቆም እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል ተብሏል። 2፤ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ታዬ አጽቀሥላሴ፣ ኢትዮጵያ ወደ አሜሪካው የአፍሪካ የቀረጥ ነጻ ንግድ ስምምነት እንድትመለስ ጠይቀዋል። ታዬ ይህን ጥያቄ ያቀረቡት፣ በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ከኾኑት ማይክ ሐመር ጋር ትናንት ባደረጉት ውይይት ላይ ነው። ታዬ እና ሐመር፣ በፕሪቶሪያው የግጭት ማቆም ስምምነትና በሱማሊያ ይሠማራል ተብሎ በሚጠበቀው የአፍሪካ ኅብረት ተልዕኮ ዙሪያ ኢትዮጵያ ባላት ስጋት ላይ ጭምር እንደተወያዩ ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር አስታውቋል። 3፤ የሕወሓት ሊቀመንበር ደብረጺዮን ገ/ሚካዔል፣ የአሜሪካ መንግሥት የፕሪቶሪያውን የግጭት ማቆም ስምምነት አፈጻጸም በመገምገም ቀጣዩን አቅጣጫ ለመወሰን ከአፍሪካ ኅብረት ጋር በቅርበት እንዲሠራ መጠየቃቸውን ሕወሓት ባሠራጨው መረጃ አስታውቋል። ደብረጺዮን ይህን የጠየቁት፣ በአፍሪካ ቀንድ ከአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሐመር ጋር በተወያዩበት ወቅት እንደኾነ ተገልጧል። ደብረጺዮን እና ሐመር፣ በስምምነቱ መሠረት መጠናቀቅ ያለባቸው ተግባራት በተወሰነ የጊዜ ሰሌዳ ውስጥ እንዲጠናቀቁና የስምምነቱ አፈጻጸምም በቀጣይነት እንዲገመገም መስማማታቸውን ሕወሓት ጠቅሷል። 4፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮ፣ ለተማሪዎች የትራንስፖርት አገልግሎት በሚሰጡ ታክሲዎች ላይ ጥሎት የቆየውን ገደብ ማንሳቱን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል። ቢሮው፣ ለታክሲዎቹ ፍቃድ የመስጠቱን ሃላፊነት ወደ ታክሲ ማኅበራት እንዳስተላለፈ ዘገባው አመልክቷል። ቢሮው፣ በከተማዋ ባሁኑ ወቅት የሚታየውን የትራንስፖርት መጨናነቅ ለመፍታት፣ በቀጣዮቹ ሦስት ወራት ውስጥ ለሕዝብ ትራንስፖርት በተለዩ መስመሮች ቁጥጥር እንደሚጀምር ገልጧል ተብሏል። 5፤ የሱማሊያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሕመድ ፊቂ፣ ኢትዮጵያ ወደ ሱማሊያ ግዛት ዘልቃ በመግባት ሉዓላዊነቷን ጥሳለች የሚባለውን ውንጀላ ማስተባበላቸውን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ፊቂ፣ ኢትዮጵያ የሱማሊያን ግዛት ጥሳ ከገባች ግን ሱማሊያ ለመመከት ዝግጁ ናት በማለት እንደተናገሩ ዘገባዎቹ አመልክተዋል። በተመድ ጸጥታው ምክር ቤት የሱማሊያ ቋሚ መልዕክተኛ፣ ኢትዮጵያ የሱማሊያን የግዛት አንድነትና ሉዓላዊነት ጥሳለች ብለው በተደጋጋሚ መክሰሳቸው ይታወሳል። 6፤ ኬንያ፣ 250 ሺሕ ዜጎቿ ጀርመን ውስጥ ሥራ እንዲቀጠሩ የሚያስችላትን ስምምነት ተፈራርማለች። ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ እና የጀርመኑ አቻቸው ኦላፍ ሾልዝ የፈረሙት ስምምነት፣ ከፍተኛ ወይም ከፊል የሙያ ሥልጠና የወሰዱ ኬንያዊያን ዘለግ ላለ ጊዜ ጀርመን ውስጥ ተቀጥረው እንዲሠሩ የሚያስችልና ጀርመንም ኬንያዊያኑ ተቀጣሪዎች ወደ አገሪቱ በቀላሉ እንዲገቡ የኢምግሬሽን ሕጓን እንድታላላ የሚያስችል ነው። የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች የሥልጠና ምስክር ወረቀት ባይኖራቸውም፣ በአገሪቱ ሥራ እንዲቀጠሩ ተፈቅዶላቸዋል። ሥራ ተቀጣሪዎቹ ሥራቸውን ከጨረሱ በኋላ በጀርመን የትምህርት ተቋማት መማር ከፈለጉ፣ ትምህርታቸውን እስኪጨርሱ የአገሪቱ መንግሥት ዘለግ ላለ ጊዜ የሚቆይ ጊዜያዊ የመኖሪያ ፍቃድ ሊሰጣቸው ተስማምቷል። [ዋዜማ]
إظهار الكل...
👍 8
اختر خطة مختلفة

تسمح خطتك الحالية بتحليلات لما لا يزيد عن 5 قنوات. للحصول على المزيد، يُرجى اختيار خطة مختلفة.