መስከረም
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ፥ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው።
10፥5 እርሱ ያ ፀሐይን አንጻባራቂ ጨረቃንም አብሪ ያደረገ ነው፡፡ የዓመታትን ቁጥር እና ሒሳብን ታውቁ ዘንድም ለእርሱ መስፈሪያዎችን የለካ ነው፡፡ هُوَ الَّذِي جَعَلَ الشَّمْسَ ضِيَاءً وَالْقَمَرَ نُورًا وَقَدَّرَهُ مَنَازِلَ لِتَعْلَمُوا عَدَدَ السِّنِينَ وَالْحِسَابَ
"ተቅዊም" تَّقْوِيم ማለት "የዘመን አቆጣጠር" ማለት ሲሆን ተቅዊም በሁለት ዐበይት ክፍል ይከፈላል፥ አንደኛው "ተቅዊሙ አሽ-ሸምሢያህ" تَّقْوِيم الشَمْسِيَّة ሲሆን ተቅዊሙ አሽ-ሸምሢያህ 365 ቀናት የያዘ የፀሐይ አቆጣጠር”solar calender” ነው። ሁለተኛው ደግሞ "ተቅዊሙል ቀመርያህ" تَّقْوِيم القَمَرِيَّة ሲሆን ተቅዊሙል ቀመርያ 354 ቀናትን የያዘ የጨረቃ አቆጣጠር”lunar calender” ነው። አምላካችን አሏህ ፀሐይ እና ጨረቃ የዓመታትን ቁጥርና ሒሳብን ማወቂያ እና መስፈሪያዎችን እንዳደረገ ተናግሯል፦
10፥5 እርሱ ያ ፀሐይን አንጻባራቂ ጨረቃንም አብሪ ያደረገ ነው፡፡ የዓመታትን ቁጥር እና ሒሳብን ታውቁ ዘንድም ለእርሱ መስፈሪያዎችን የለካ ነው፡፡ هُوَ الَّذِي جَعَلَ الشَّمْسَ ضِيَاءً وَالْقَمَرَ نُورًا وَقَدَّرَهُ مَنَازِلَ لِتَعْلَمُوا عَدَدَ السِّنِينَ وَالْحِسَابَ
በጨረቃ አቆጣጠር አዲስ ጨረቃ ሲታይ አዲሱ ወር ሙሐረም የወሮች መባቻ(መጀመሪያ) ሆኖ ይጀምራል፥ "ሙሐረም" مُحَرَّم የሚለው ቃል "ሐረመ" حَرَّمَ ማለትም "ቀደሰ" "አከበረ" ከሚል ሥርወ-ቃል የመጣ ሲሆን "የተቀደሰ" "የተከበረ" ማለት ነው። ሙሐረም ክብር ያለው የአሏህ ወር ነው፦
ጃሚዒ አት-ቲርሚዚይ መጽሐፍ 8 ሐዲስ 59
አቢ ሁረይራህ”ረ.ዐ” እንደተረከው፦ “የአሏህ መልእክተኛ”ﷺ” እንዲህ ብለዋል፡- ”ከረመዷን ቀጥሎ ከጾሞች ሁሉ በላጩ የአሏህ ወር የሆነው ሙሐረም ነው። عَنْ أَبِي هُرَيْرَةَ، قَالَ قَالَ رَسُولُ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم “ أَفْضَلُ الصِّيَامِ بَعْدَ صِيَامِ شَهْرِ رَمَضَانَ شَهْرُ اللَّهِ الْمُحَرَّم
ሙሐረም "የአሏህ ወር" የተባለበት አሏህ ሰማያትንና ምድርን በፈጠረበት ቀን አንድ ተብሎ ወር የተጀመረበት ወር ስለሆነ ነው። “ወር” የሚለው ቃል በነጠላ “ሸህር” شَهْر ሲሆን በነጠላ ቁጥር በቁርኣን 12 ውስጥ ጊዜ ተጠቅሷል፥ የሚያጅበው የወሮች ቁጥር አሏህ ዘንድ በአሏህ መጽሐፍ አሥራ ሁለት ወር ነው፦
9፥36 የወሮች ቁጥር አላህ ዘንድ በአላህ መጽሐፍ ውስጥ ሰማያትን እና ምድርን በፈጠረበት ቀን አሥራ ሁለት ወር ነው፡፡ إِنَّ عِدَّةَ الشُّهُورِ عِندَ اللَّهِ اثْنَا عَشَرَ شَهْرًا فِي كِتَابِ اللَّهِ يَوْمَ خَلَقَ السَّمَاوَاتِ وَالْأَرْضَ
አሏህ ሰማያትን እና ምድርን በፈጠረበት ቀን አሥራ ሁለት ወር ሲሆን አሏህ ሰማያትን እና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በስድስት ቀናት ውስጥ በእርግጥ ፈጥሯል፦
50፥38 ሰማያትን እና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በስድስት ቀናት ውስጥ በእርግጥ ፈጠርን፡፡ وَلَقَدْ خَلَقْنَا السَّمَاوَاتِ وَالْأَرْضَ وَمَا بَيْنَهُمَا فِي سِتَّةِ أَيَّامٍ
በግሪክ ኮይኔ "ሄክሳ" ἑξα ወይም "ሔክስ" ἕξ ማለት "ስድስት" ማለት ሲሆን "ሔሜራ" ἡμέρᾱ ወይም "ሄሜሮስ" ἥμερος ደግሞ "ቀን" ማለት ነው፥ በጥቅሉ "አክሲማሮስ" ማለት "ስድስት ቀናት" ማለት ሲሆን አክሲማሮስ ስለ ስድስት ቀናት አፈጣጠር የሚያወራው ትምህርት ነው። በ4ኛው ክፍለ-ዘመን ከ 367-403 ድኅረ-ልደት የቆጵሮስ ኤጲጵ ቆጶስ የነበረው ኤጲፋንዮስ ያዘጋጀው መጽሐፍ እራሱ አክሲማሮስ ይባላል።
ከ 180 እስከ 222 ድኅረ ልደት ድረስ ለ 42 ዓመታት የአሌክሳንድርያ ፓትርያርክ የነበረው ድሜጥሮስ የቀመረው የዘመን ቀመር “አቡሻኽር” ወይም “ባሕረ-ሐሳብ” ሲባል በዚህ የዘመን ቀመር ላይ ስለ “አዕዋዳት” ይናገራል፥ “አዕዋድ” ማለት “ዖደ” ማለትም “ዞረ” ከሚል የግዕዝ ቃል የተገኘ ሲሆን “ዙረት” ማለት ሲሆን በየጊዜው እየዞረ የሚመጣ ማለት ነው።
የፀሐይ አቆጣጠር የሚዞረው 365 ቀናት የያዘው ሲሆን የጨረቃ አቆጣጠር የሚዞረው ደግሞ 354 ቀናት የያዘው ነው፥ የጨረቃ አቆጣጠር 11 ቀናት በመዘግየት ከፀሐይ አቆጣጠር ሲዘገይ "ሙሐረም" ወደ ኃላ ሲሆን ከፊት ለፊቱ ያለው ስሌት "መስከረም" ይሆናል። በአይሁድ የመጀመሪያው ወር ኒሳን ማለትም አቢብ ወር ሲሆን ከዚያ ሰባተኛው ወር ቲሽሬ ነው፦
ዘጸአት 12፥2 ይህ ወር የወሮች መጀመሪያ ይሁናችሁ፤ የዓመቱም መጀመሪያ ወር ይሁናችሁ።
ከኒሳን ወር ሰባት ወር ስንቆጥር "ቲሽሬ" የሚባለው ወር መስከረም ነው፥ "ቲሽሬ" תִּשְׁרִי ማለት "መጀመርያ" ማለት ነው። አይሁዳውያን ይህንን ወር "ሮሽ ሀ ሸናህ" רֹאשׁ הַשָּׁנָה ማለትም "የዓመቱ ርእስ፣ ጅማሮ፣ ራስ፣ አውራ" በማለት አዲስ ዓመት ይጀምራሉ። "ቲሽሬ" ወይም "ሮሽ ሀ ሸናህ" በፀሐይ አቆጣጠር "መስከረም" እና በጨረቃ አቆጣጠር "ሙሐረም" መሆኑን ፍንትው እና ቁልጭ አርጎ ያሳያል።