በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ዘለዓለም ሥላሴ።
እንኳን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል (#ጼደንያ) በሰላም አደረሳችኹ።
(ታሪክ) በሀገረ ደማስቆ በጼዴንያ ክፍል መሪና በምትባል ቦታ የተከበረችና የተመረጠች ማርታ የምትባል ደግና ትሑት ሴት ነበረች። እንደ አብርሀም የእንግዳ መቀበያ የተለየ ቤትን ሠርታ እንግዶችን ትቀበል ነበር። በቤቷ ካደሩት እንግዶች አንዱ የሆነ አባ ቴዎድሮስ የተባለ ኢትዮጵያዊ አባት የጌታን መቃብር ለማየት ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ ወንጌላዊ ሉቃስ የሣላትን የእመቤታችን ሥዕል እንዲያመጣላት ቃል አስገባችው።
ይህ አባት የጌታን መቃብር ተሳልሞ ሥዕሊቱን ረስቶ ሲመለስ "የገባኸውን_ቃል_እረሳህ" የሚል ድምጽ ከሰማይ ሰማ። ተመልሶ ሄዶ ቅዱስ ሉቃስ የሣላትን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ገዝቶ ጉዞውን እንደጀመረ ከመንገድ አንበሳ መጣበት። አባ ቴዎድሮስ ታላቅ ድንጋጤ ሲደነግጥ ከሥዕሏ እንደ መብረቅ ያለ ድምጽ ወጥቶ አንበሳውን አሳደደው፤ በዚሀ ጊዜ በጣም ተደሰተና ጥቂት መንገድ እንደሄደ ደግሞ ሽፍታ መጣበት። ደነገጠ፤ በዚያም ጊዜ በክንዱ ከያዛት ሥዕል በድጋሚ የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ድምጽ ወጣና ሽፍታውን እንደ አንበሳው አሳደደው። አባ ቴዎድሮስም እጅግ በጣም ተደሰተና የተደረገለትን ተአምር እያደነቀና እየተገረመ ጉዞውን ቀጠለ። አባ ቴዎድሮስ ሥዕሏ ካደረገችው ተአምር የተነሣ እንዲህ_ያለችውን_መድኃኒት_ለራስ_ያደርጓታል_እንጂ_ለሰው_ይሰጧታልን? ብሎ ወደ ጼዴንያ የሚወስደውን ትቶ በሌላ መርከብ ተሳፍሮ ሲሄድ ሥዕሊቱ ነፋስ አምጥታ ወደ ማርታ ቤት ወሰደችው። ይህም አባት ወደ ማርታ ቤት በእንግድነት የሚገቡ የሚወጡ ብዙ ናቸውና አታውቀኝም ብሎ ገብቶ አደረ፤ ጠዋት ተነሥቶ የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ለማርታ ሳይሰጥ ወጥቶ ሲሄድ የአጥሩ በር ይጠፈዋል፤ መሄድም ይሳነዋል ሲደከም ውሎ ከማርታ ቤት ገብቶ አደረ። ይህ ሲሆን ማርታ በትዕግሥት ታስተውለው ነበር። እንዲህ እየሆነ ሦስት ቀን ሞላው መውጣት ተሳነው ማርታ አባቴ_ለመሄድ_ትፈልጋለህ_መሄድ_ግን_አትችልም በአንተ የማየው ምንድን ነው? ስትለው እርሱም የደበቃትን ኃጢአቱን ገልጦ ነገራት፤ የእመቤታችን ሥዕል ያደረገችለትን ገቢረ ተአምር መስክሮ የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ከክንዱ አውጥቶ ሰጣት። ማርታም ሰግዳ እጅ ነስታ ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ስትገልጠው ከሥዕሏ ከፊቷ ሥጋ_እንደለበሰ_ወዝ_ወጣ። ሕሙማን ወዙን ሲቀቡ ይፈወሱ ነበር። <<ወይእቲ ሥዕል ትመስል ልብሰተ ሥጋ፤ ወያንጸፈጽፍ ሐፍ እምኔሃ (ሥዕሏንም ሥጋ የለበሰች ከፊቷም ወዝ የሚንጸፈጸፍ አስመስሎ ይስል ነበር)>> እንዲል። ማርታም ለሥዕሏ የጸሎት ቤት አሠርታ ከዚያ በማስቀመጥ በቀንና በሌሊት ዘወትር መብራትን በማብራት በቀኝና በግራ እጅ እየነሳች እሰከ ዕለተ ሞቷ የምታበራ ሆነች። እሷም በሰላም አርፋ በብርሃን እናት አማላጅነት መንግሥተ ሰማያትን ወረሰች። አባ ቴዎድሮስም ያችን ሥዕል እድሜ ልኩን ሲያገለግል ኑሮ በሰላም አረፈና በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት መንግሥተ ሰማትን ወረሰ።
ንጉሥ ሰሎሞን ለታቦተ ጽዮን ማደሪያ የሚሆን ቤተ መቅደስን እንደሠራ ሁሉ (፪ኛ ነገ.፭-፲፯) ቅድስት ማርታም ለእመቤታችን ሥዕል ቤትን አሠርታ አክብራ አኖረቻት። ሌሊትና ቀንም በቀኝና በግራ መብራትን ታበራላትና እየሰገደች እጅ ትነሣት ነበር።
በእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም_ሥዕል_ተአምር_ለክብር_የበቁ_ቅዱሳን_ከብዙ_በጥቂቱ፦
፩. ሊቀ_ጳጳስ_አብርሃም_ሶርያዊ
በግብፅ አገር ሊቀ ጳጳስ ሲሆን ሁለት ሚስት የአገባችሁ ፍቱ እያለ ሲያስተምር አንድ ክርሰቲያን አልታዘዝም አለ። ከቤቱ ሂዶ በሩን ዘግቶ አልከፍትም አለ። ይህንን በማድረጉ ተቀሰፈ። ይህንን ያየ የዚያ ሰው ጓደኛ በአሕዛብ ንጉሥ ነገር ሠራበት። ንጉሡ አባ አብርሃምን አስጠርቶ በወንጌል ውስጥ የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እምነት ቢኖራችሁ ተራራ ማፍለስ ትችላላችሁ የሚል አለ እንደ? ብሎ ጠየቀው አዎ_አለው፤ አድርገህ አሳየኝ አለው፤ ሦስት ቀን ስጠኝ አለውና ሰጠው። ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ሄዶ ቢማጸን በሦስተኛው ቀን ከሥዕለ ማርያም ድምጽ ሰምቶ የሚያደርገውን ነግራው ተራራውን ወደ ሰማይ ከፍ አድርጎ ለንጉሡ አሳይቶታል።
፪. ቅዱስ_ማርቆስ_ዘቶርማርቅ
በሮሜ አገር ለዐሥር ዓመት ድኃ ሳይበድል ፍርድ ሳያጓድል በድንግልና ሕይወት ሕዝብን አስተዳደረ። ምእመናንም ከፍቅራችው ጽናት የተነሣ ሚስት አግባ አሉት። እሱም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ሄዶ ቢማጸን ከሥዕለ ማርያም ድምጽ ወጥቶ ንግሥናህንና ዓለምን ትተህ ገዳም ግባ አለችው። እሱም ሳይውል ሳያድር ንግሥናውንና ዓለምን ትቶ ገዳመ_ቶርማርቅ በገድል በትሩፋት ኑሮ በሰላም አርፎ በእመቤታችን አማላጅነት መንግሥተ ሰማያትን ወረሰ።
፫. አባ_ጽጌ_ድንግል
ማኅሌተ ጽጌን የደረሰው ለዚህ ክብር የበቃው ከአይሁድ እምነት ወደ ክርስትና ሃይማኖት በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ገቢረ ተአምር ነው።
እኛ ምእመናን እንደ ቅድስት ማርታ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል የጸሎት ቤት አዘጋጅተን መብራትን እበራን ስንወጣ ስንገባ እጅ እየነሳን መሆን ይጠበቅብናል። እንደ ቅዱስ ኤፍሬም ውዳሴዋን በየዕለቱ እንደ ምግብ እየተመገብን፤ እንደ ልብስ እየተጐናጸፍን፤ እንደ ቅዱስ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴዋ እንድንቀደስ፣ እንደ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የፍቅሯን ማዕበል በልባችን እንድታሳድርብን፣ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ አፈ በረከት እንድታሰኝን፤ እንደ አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን ከእግዚአብሔር የተጣሉትን ለማስታርቅ መንገድን እንድትመራን፤ እንደ ቅድስት ማርያም ግብጻዊትና እንደ ሶፍያ እመ ምኔት ከዝሙት አውጥታ መንኖ ጥሪት(ዓለም)፣ ለብሕትውና ሕይወት እንድታበቃን እግዚአብሔር ይፍቀድልን።
ምንጭ
✔ማኅሌተ ጽጌ ንባቡና ትርጓሜው፣
✔ተአምረ ማርያም፣
✔መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ መስከረም
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ‼